የማን ናት?
ኢትየጵያ የማን ናት?… እረ ለመሆኑ ያች አገር የማን ናት ?
…መሣሪያ የታጠቁ፣ በሰውር የተደራጁ የጥቂት ሰዎች ንብረት ? ወይስ የዜጎቹዋ? የኑዋሪዎቹዋ? የሕዝቦቹዋ?
ወይስ የአንተና የእኔ? …የእሱዋና የእነሱ? የዚያና የዚህ? ወይስ የእገሌና የእገሊት? የስደተኛው ወይም ከየትም ተነስቶ በጠበንጃ የያዛት:- ብዙዎቹ እንደሚሉት „የሸፍታው ሁሉ“?
የማን አገር ናት ይህቺ ማንም ትላንትም ዛሬም የሚቀልድባት ኢትዮጵያ?
የሻቢያ ወይስ የወያኔ? የኦነግ ወይስ የኦጋዴን? የአማራ ወይስ የጉራጌ? የወታደር ፖሊሱ ወይስ የጦር ሠራዊቱ? ወይስ ደግሞ የቸርቻሪ ነጋዴ?
የማን ናት ለመሆኑ ይህች መከራ የገባችው አገር?
የ ሁለቱ ግለሰቦች የኢሳያስ አፈወርቂና የመለሰ ዜናዊ ? … የሞተላት ሰው ወይስ የሸጣት?
ይህ እንዳይባል አንደኛው ታሞአል። ሌላው አርፎአል። ሁለቱም፣ በዚያውም ድርጅቶቹ ደግሞ ተጣልተዋል።
የእነ አዜብና የእነ ስብሃት ነጋ ወይስ የእነ አርከበና የእነ አባ ዱላ? ወይስ የእነ አንዳርጋቸውና የእነ ብርሃኑ ነጋ? የመራራ ጉዲና እና የእነ ነጋሶ ጊዳዳ? የእነ ኃይሉ ሻውል ወይስ የእነ መስፍን ወልደ ማሪያም? የእነ ቡልቻ ደመቅሳ ወይስ የ…?
ኢትዮጵያ የእነሱም ናት እንዳይባል ምንም ዕይነት ማረጋጫጫ ነገር አይታይም። ታዲያ ባለቤቱዋ ዛሬ ማን ነው?
የመኢሶንና ኢህአፓ፣ የኢዲዩና የደርግ፣ የእነሱ ናት ማለት እንችላለን?
ይህም እንዳይባል፣ የእነሱም ናት ብለን እንዳንከራከር፣ እነዚህ ሦስቱም አራቱም ድርጅቶች ሳይስማሙ ተፋጅተው፣ ተበታትነው የትም ወድቀው ቀርተዋል። ታዲያ አለሁ አለሁ የሚለው፣ ያ በሕይወት ያለው የዚያ የመንግሥቱ ኃይለማሪያምና የኢሠፓ ትሆን?
ወይስ ሳይታሰብ ብቅ ብለው የእህአዴግን ማዕከላዊ ኮሚቴ ያስደነገጡት የጠቅላይ ሚኒስትሩ የኃይለ ማሪያም ደሳለኝ ?
የማን ናት ይህቺ የፈረደባት አገር?
የኃያላን መንግሥታት ናት:- የአሜሪካን ወይስ የአውሮፓ?… የጀርመን ናት ወይስ የጣሊያን? የሳውዲ ንጉሥ ወይስ የአረብ አገር ቱጃሮች? የአክራሪ እስላሞች? ወይስ የጴንጤዎች? የፕሮቴስታንቶች ወይስ የካቶሊኮቹ? ወይስ የራሻ?
ለመሆኑ ይህቺ አገር ኢትዮጵያ የማንናት?
የክርስቲያኖቹ ብቻ እንዳይባል እስላሞችም፣ አይሁዶችም፣ ሃይማኖት የለሽ „አሕዛቦችም“ ከብዙ ዘመን ጀምሮ አብረው አንድ ላይ ይኖሩባታል። ታዲያ የማን አገር ናት አሁን? ለመሆኑ አንድ ባለቤት አላት? ወይስ የላትም? ቢያንስ ተቆርቋሪ ቡድን?
የበረንዳ አዳሪዎችና የማጅራት መቺዎች ናት? የሥራ አጦችና የሥራ ፈት ወጣቶች? የለማኞችና የከተማ ድሆች? የአጋዚያንና የሰላዮች? ወይስ የሕንድና የቻይናዎች? ወይስ የአላሙዲና የካራቱሪ?… የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች? ወይስ የዩኒቨርስቲ ጎልማሶች? …የአስተማሪዎች ወይስ የሠራተኞች?
ግራ ገብቶናል:- የማን አገር ናት ያቺ ኢትዮጵያ?
ዕውነት እንደሚባለው „የቺታና“ (ይህ ነገር ከየት እነደመጣ አናውቅም እንበል!) ወይስ „የጥቁር አንበሳ „ ? ወይስ የአራዳ ልጆች እንደሚሉት „የቺስታና“ (ይህም ቃሉ ግራ የሚያጋባ ነው) የጫት ቃሚዎች?… የሰካራም ወይም የዝሙተኞች …የአታላይና የአጭበርባሪዎች፣ … የሙስና ተቀባዮችና እና የባለጌ ልጆች ?
እረ ይህን የሚያውቅ ሰው አለ ወይ! ?- …የማን ናት…ይህቺ አገር፣ ስምዋን እንኳን ለመናገር አንዳንዶቹ የሚጠየፉት ያቺ ኢትዮጵያ?
የሰላይና የቀስቃሽ፣ የመንደር አስፈራሪ ካድሬዎች፣ የቀበሌ ሰዎች „አገር ነው“ እንዳይባል እነሱን የቀጠረ አንዳች ኃይል ከጀርባቸው አለ። ገንዘብም የሚሰጣቸውም ሌላ መንግሥት አለ።
ታዲያ ምንም የማያውቁ የመሓይሞች አገር ትሆን? … ወይስ ፊደል የቆጠሩ የተማሩ ሰዎች ዝም ብለው የሚያዩበት አገር? የገበሬዎች ወይስ የግንበኞች?
ወይስ እንዲያው እንደሚባለው የመሣፍንቶቹ ሐብት ትሆን?
የመሣፍንቶችና የመኳንንቶች አገር ናት፣ … እንዳይባል እነሱም ታርደው በጥይት ተደብድበው፣ የተቀሩት ጃጅተው፣ ሌሎቹ አርጅተው ሞተዋል። አንዳንዶቹ መቃብርም እንኳን የላቸውም።
የቄሶችና የካህናቶች፣ የጥበበኞቹ ሐብት ናት … እንዳይባል እነሱም እራሳቸው፣ ገዳማቸው ሳይቀር አሁን ተደፍሮአል። ታዲያ የማን ናት ይህቺ ጥንታዊ አገር?
የእሳላሞቹ ትሆን?
ኢትዮጵያ የማን ናት? ብሎ ዛሬ መጠየቅ „አሜሪካ የማን ናት?“ ብሎ ደፍሮ ከመጠየቅ ምንም አይለይም። ይህ ከሆነ ደግሞ ለመሆኑ አሜሪካ የማን ናት? ….ማን ነው ባለቤትዋ ….ዱሮም አሁንም?
….እንግሊዚስ ?
ይህ ነገር፣ ታላቁዋ ብርታኒያ እሱዋስ የማን ናት ብሎ ደፍሮ ከመጠየቅ አይለይም። ለመሆኑ …ብራዚልስ፣ ሳውዲስ፣ ኩዌት፣ ሩሲያ፣ ናይጄሪያና ጋና፣ ጀርመንስ ? …ታይዋንና ደቡብ ኮሪያ …ጃፓን እና ሕንድስ እነሱስ የማን ናቸው? እንደማለትም ነው።
ለካስ ፈረንሳይም አለች። እሱዋስ ብትሆን የማን ናት?
ብዠ ከአላለብን „ኢትዮጵያ የማን ናት?“ ለሚለው ጥያቄ እላይ ለተጠቀሱት አገሮች ከምንሰጠው መልሶች፣ የእኛይቱዋም ፍጹም አይለይም።
ግልጽ ደግሞ እንሁን ። ሌላም ጥያቄ አለ።
ለመሆኑ የዛሬዋ ሰሜን ኮሪያ የማን ናት? ብለን ይህን ጥያቄ አንስተን እራሳችን ብንጠይቅ፣ መልሱ አንድ አስተዋይ ሰው እንደሚረዳው ቀላል ነው።
እንግዲህ በዚህ አቀራረብ ቀስ እያልን አሁን ግልጽ እየሆን የመጣን ይመስላል። ደግሞ በዚህ ጉዳይ ላይ ግልጽም መሆን ያስፈልጋል።
በዚህ ሎጅክ ከሄድን ደግሞ፣ በእሱም መሄድ አለብን፣ በዚያም እንሂድ:- …ኪዩባስ ዛሬም፣ ትላንትም፣ ድሮም፣ የማን ነበረች?… ቻይናስ? …ታላቁዋ ቻይናስ አሁን የማን ናት? …ሶሪያስ? ግብጽስ?
ቀጠል አድርገን እዚያው ላይ ሱማሊያስ የማን ናት? የሚለውን እናንሳ። ይህን ጥያቄ ስናነሳ ደግሞ ትንሽ ለየት ያለ መልስ እናገኛለን።
ለምን ለየት ይላል?
አንዳንዱ እንደ ሰሜን ኮሪያ ያለ አገር፣ አገሪቱን ማርኮ ሕዝቡን አፍዞ „…ዙፋኑን„ ለልጅ ልጁ ከማውረስ አልፎ፣ ይህ አልበቃው ብሎ ሰውንም አደባባይ ጠርቶ (አንዱ ዘመዳቸው በድንገት ወይም በስካር ሲሞትባቸው፣ የቀልድ ዓለም ውስጥ ገብተናል) በሰልፍ እንዲያለቅሱ፣ በትዕዛዝ እንኳን ሳይቀር እያስፈራሩ በጥሩምባ እንደ ዕድር እየጠሩ፣ ሕዝቡን እነሱ ኮሚኒስቶቹ እዚያ በቴሌቪዥን እንዳየነው እስከ ማስለቅስ – ጠግበው፣ አልበቃ ብሎአቸው- እስከዚያ ድረስ ሄደዋል።
ለመሆኑ ያለነው በድንጋይ ዳቦ ዘመን ወይስ በ21ኛው ክፍለ-ዘመን?
ይህ ሰውን አደባባይ ጠርቶ የማስለቀስ ነገር፣ የአፍሪካ ዋና ከተማ አዲስ አበባም ገብቶአል።
ሰሜን ኮሪያ የማን ናት?
ኪዩባ ላይ አንዴ ሥልጣኑ (እነሱ ይህን አብዮት ይሉታል) የወንድማማቾቹ እጅ ገብቶ፣ እንደ ሳውዲ አረቢያ ነገሥታት፣ እዚያው መዳፋቸው ውስጥ እንዲቀር ተደርጎአል።
ታላቅና ታናሽ ወንድማማቾች ….ሥልጣኑን እንደ ቅብብሎሽ የዱላ እሩጫ፣ ማንንም ሳይፈሩ፣ ማንም ሳይስቅባቸው፣ እሰከ አሁን ድረስ ይቀባበሉታል ። ነገ ደግሞ ማን ያውቃል ልጆቻቸውም እንዲደርሳቸው ይደረጋል። ሓቫና ላይ ይወርሱም ይሆናል። ታዲያ ኪዩባ የማን ናት?
በሱማሊያ የምናየው ግን ሌላ ነገር ነው።
ለእኛ ለኢትዮጵያኖች የተደገሰው ድግስም እሱ ይሆናል!
ማንም የመንደር ልጅ ዝናሩን ከታጠቀ የአካባቢው አምባ „አለቃ“ ነው። አለቃም ሁኖ ማንም ሳይይፈራ፣ ማንም ሳይደፍረው እንደ አንድ „አምባገነን አገረ – ገዢ“ አካባቢውን እሱ እዚያ ይቆጣጠራል። ያ ልጅ ደግሞ ከጓደኞቹ ጋር ዘመድ አዝማዱን ሳይቀር ያሸብራል። ተው የሚል ተቆጪም አባትም እናትም የመንደር ሽማግሌም የለም። ይህ ከሆነ ደግሞ ታዲያ ሱማሌ ዛሬ የማን ናት?
በግብጽ ወታደሩ በአንድ በኩል፣ በሌላ በኩል የሞስሊም ወንድማማቾች አገሪቱም፣ ሐብቱም፣ ሕጉም፣ አለባበሱም፣ መሬቱም ግዛቱም „…የእኔ ነው ….የለም የአንተ አይደለም“ ብለው ተከፋፍለው ይተናነቃሉ። አሁን ግብጽ የማን ናት?
ወጣ ወረደ ለምን ስለሌሎቹ እንቸገራለን :- ኢትዮጵያ ለመሆኑ የማን ናት? ብለን እራሳችንን እንጠይቅ።
ለዚህ ጥያቄ በቅርቡ የተሰራጩት የእነ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ትንተናዎችና የሌሎቹ አቀራረቦች ግልጽ አድርገውልናል።
ይህ ጉዳይ ግን ጎበዝ፣ ለአዳማጭ ጆሮ አዲስ ይመስላል እንጂ ለኢትዮጵያ፣ አዲስ አይደለም።
ከእነ አንዳርጋቸውም በፊት ሆነ በዚያኑ ጊዜ ሌሎቹ አዲስ አበባ ወርደው ስብሰባ አካሂደው ቢሮ ከፍተው ከተመለሱ ወዲህ የአሥመራው አቶ ኢሳያስና የአዲስ አበባው አቶ መለስ ያን አካባቢ (አንዱ ሌላውን በጦር ስለሚፈልገው) ወዴት ጎትተው ለመክተት እንደ ፈለጉ በግልጽ ያዳመጣቸው ከአለ፣ እነሱ በግልጽ አሳይተውናል።
ከእነ አቶ አንዳርጋቸው ንግግር መረዳት እንደሚቻለው „…አቶ ኢሳያስ የኢትዮጵያን ሕዝብ ከግንቦት ሰባት ጋር ሁኖ፣ አንድ ላይ ቁሞ ከአምባገነኑ የወያኔ የጭቆና መዳፍ አውጥቶ፣ የዲሞክራሲ ሥርዓት እነሱ ለእኛ ሊያመጡልን ይፈልጋሉ።“
ይህ እውነት ነው? ይህ እንዲያው ዝም ብሎ ሊሆን ይቻላል? ይህ ሁሉ ቲያትር ወዴት ነው?
እንደዚሁ ወደ አዲስ አበባ ቀደም ብለው የዘለቁት የኢሳያስ ተቃዋሚዎች ቡድኖች ደግሞ-ጀበሃዎቹና ሌሎች በርካታ ድርጅቶችን አቅፈው- „ከትግራይ ሕዝባዊ ወያኔዎች ጋር ሁነው እንደ ላይኞቹ የኤርትራን ሕዝብ ከአረመኔው የሻቢያ አምባገነን አገዛዝ ነጻ እነሱን ሊያወጡአቸው -እንደ ተነበበው ይፈልጋሉ። ይመኙላቸዋል። “ይህኛውስ ድራማ ምንድነው? ፖለቲካ ነው?
እስከዚህ ድረስ ታሪኩ „በቲዎሪ“ ደረጃ ጥሩ ነው። ታሪክ ግን ሌላ ነገር ያስተምረናል።
ባህር ላይ ወድቆ ወሃ እንዳይበላው ከሚታገል አንድ ሰው ታሪክ አንጀምር።
ይህ ሰው ነፍሱን ለማዳን -የመካከለኛው ምሥራቅ ሰዎች እንደሚተርኩት ከሆነ- ከስጥመት ለመዳን እባብ አጠገቡ ከአየ፣ ከአገኘ ይህ ሰው እሱን ከመጨበጥ አይመለስም። ይጨብጣል፣ ይላሉ። ነገሩ የነፍስ ነገር ሲሆን ባህር ላይ እንኳን አንድ እባብ፣ የዘንዶም አንገት ወይም የአዞ ጭራ ይዞ ለመትረፍ እንደመሞከርም ነው።
ወይም ሊበሉት ከሚያሳድዱት ተኩላዎች አፍ አምልጦ የጅቦች ዋሻ ውስጥ ነፍሱን ለማዳን ዘሎም እንደሚገባ ሰው ዓይነት ነው። ይህ ሰው ግን በዚያም በዚህም ከገባበት ጣጣ አይተርፍም።
ፖለቲካ ግን፣ የአንድ ነገር የገባው የፖለቲካ ሰው ጉዞ ግን፣ እባብ ከሚጨብጠው፣ ወይም አዞ ከሚጋልበው ወይም ተኩላ ሸሽቶ የጅብ ዋሻ ዘሎ ከሚገባው ከእሱ ሥራ ፍጹም የተለየ ሌላ ነገር ነው። እነዚህ እላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎችም ነገሮችን ሰንጥቀን ከፋፍለን እንድናይ የሚረዱን ትምህርቶች ናቸው እንጂ፣ „እኔ እከሌን ለመጣል ከሰይጣንም ጋር ቆሜ አብሬ ለመሥራት ዝግጁ ነኝ የሚያሰኝ….“ አይደለም።
አንደኛው እላይ የተጠቀሰው እባብ የሚያቅፈው ሰው ምሳሌ፣ መውጫ መግቢያ ያጣ ሰው ሥራ ወዴት እንደሚወስድ ለማሳየት ነው። ፖለቲካ ግን የጥድፊያ የጭንቀት ሥራ ውሳኔ ሳይሆን ረጋ ተብሎ አውጥቶ አውርዶ ተመካክሮ የሚሰራ የጭንቅላት ሥራ ነው።
በሁለቱ በተጨነቀ ሰው እርምጃና ውሳኔ እና ረጋ ተብሎ በሚሰራው የፖለቲካ ሥራ መካከል ደግሞ ትልቅ የልዩነት ዓለም አለ።
አምባገነኑ ስታሊን ምሥራቅ አውሮፓን ከሒትለር ፋሺዚም „ነጻ-ሲያወጣ በእሱ ቦታና በእሱ ፋንታ ምን እንደ ተከለ“ የአለፈው ሃምሳ አመት ምስክር ነው። ግን ስንት ሰው ለመሆኑ እንደዚህ ዓይነቱን አካሂድ ተገንዝቦአል? ለመሆኑ ይህን የተገነዘቡስ ሰዎች በመካከላችን አሉ ወይ ? ከአሉስ እነሱ ምን ይላሉ?
እነዚህን ቀደም ሲል የወጡትን ጥናቶች የተከታተለ ሰው ምን ዓይነት ትምህርት አግኝቶአል?
ጉዳዩ ሌላም ነገርን ያስታውሰናል።
ዱሮ በንጉሡም ዘመን ሆነ በደርግ ጊዜ „ለኢትዮጵያ ዲሞክራሲ እናመጣለን“ ብለው በስውር የተለያዩ ወጣቶች ተነስተው ሲደራጁ (አሁን ስማቸውን መጥቀስ አስፈላጊ አይደልም) እነሱ አንድ ቀን ሥልጣኑን ሲይዙ (ምንም እንኳን የፖለቲካ ፕሮግራማቸው ላይ አላማቸውና ግባቸውን በትክክል ቢያሰፍሩም) እነሱ አምባገነኖች ሁነው ፕሬሱን አፍነው፣ የሕዝብ መብት ረግጠው ሌላውን አባረው፣ ጓደኞቻቸውን አሥረው ወይም ገድለው፣ ኢትዮጵያን ከፋፍለው ይህን ሁሉ አመታት አለርህራሄ እኛን „ይገዙናል“ ብሎ የገመተ ሰው የለም። አልነበረም። በጭፍን ከእሳቸው፣ ከንጉሡ የተሻለ ይመጣል ተብሎ ሳይጠየቅ ዝም ተብሎ ተገባበት።
ደርግና መንግሥቱ ኃይለ ማርያም በአንድ በኩል፣ ወያኔና ሻቢያ በሌላ በኩል፣ ከእነሱ መካከል ደግሞ ሌሎች ድርጅቶች ብቅ አሉ።
ምንድ ነው የሆነው?
ከንጉሡ የተሻለ ሥርዓት ኢትዮጵያ አገኘች? ሰበአዊ መብቶች፣ የግለሰብ ነጻነቶች በኢትዮጵያ ተከበሩ?
ከደርግ አምባገነን ሥነ-ሥርዓት ና ከመንግሥቱ ኃይለ ማርያም የተሻለ መንግሥት ይመጣል፣ ወያኔንና ሻቢያን „እንደግፍ“ ተባለ?
ምን ድነው የተገኘው፣ ምንድነው የሆነው በመጨረሻው?
የሆነው ግን (ያላወቃችሁ ከአላችሁ ዛሬውኑ እርማችሁን አውጡ) ሌላ ነገር ሳይሆን፣ በትክክል የታጨደውም የተሰበሰበውም የአንድ ፓርቲ አምባገነን ሥርዓት እና ለሁለት የተገመሰች ኢትዮጵያን ነው።
እንኳን እነሱ ሥልጣን ላይ የወጡት ቡድኖች ቀርተው፣ እነሱን „ታግለን ኢትዮጵያን ነጻ እናወጣለን „ የሚሉት ኃይሎችም (ዛሬ ኤርትራዊ ነን ይበሉ ወይም ኢትዮጵያዊ፣ ወይም ሌላ ስም ይያዙ) ከዚህ አስተሳሰብና አመለካከት ብዙዎቹ ፈቀቅ እንኳን አላሉም።
ሌላም ጥያቄ እዚሁ ላይ ማንሳት ይቻላል።
ከኢሳያስ አፈወርቂ ጋር አብሮ ቆሞ ኢትዮጵያን ከወያኔ የአምባገነን መዳፍ የሚያወጣ ሰው፣ እሱ ለመሆኑ „ዲሞክራት ነው“ ብሎ መገመት ይቻላል? እኛ ያስቸግራል እንላለን። ይኽ የ “የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው” ፍልስፍናና ዘይቤ (ይህን አስመልክተን ሰሞኑን አነጋጋሪ ስለ ሆነው ዱብእዳ ባጭሩ አስተያየታችንን ሰጥተንበታል፤ እዚሁ መጽሔት ውስጥ፤ ተመልከቱት) ባለፈው ግማሽ ምዕተ ዘመን ኢትዮጵያን የት ዛሬ እንዳደረሳት፣ እንኳን የፖለቲካ አዋቂ ነኝ የሚል ቀርቶ፣ ተራ ሰውስ ማስተዋል እንዴት ይሳነዋል? ወይስ ሌላ ጠለቅ ያለ የስነ ልቦና ምርምር ውስጥ እንግባ፤ የለም እዚሁ ፖለቲካው ላይ እናቁምና፥ እንቀጠል። አንድ ነገር ግን እናንሳ። ፖለቲካ ሞራል አያውቅም ይባላል። ቢያንስ ግን ፖለቲካ (ካንቲያኖች እንደሚሉት) ለሚሰራው ሥራ ዝም ብሎ መጋለብ ሳይሆን፣ ለሚመጣው ትርምስና ጥፋት ( የተተለመ ነገር ሁል ግዜ ግቡን አይመታም፣ እንዲያውም የተገላቢጦሹን ያጭዳል) ኃላፊነቱንም አውቆ መቀበልም ይኖርበታል።
ኢሳያስም አንዱ እንዳለው፣ „…አላበደም ገንዘቡን፣ ሐብቱን፣ ንብረቱን አፍሶ በል እንግዲህ ኢትዮጵያን እንደፈለግ አድርግ ብሎ መርቆ ስሞ የሚሸኘው…ሰው አይደለም። ሊሆንም አይችልም። እሱ ቢፈልግ ድርጅቱ አይፈልግም “።
ሕዝባዊ ወያኔም በተቃራኒው „…አላበደችም የኢሳያስን ተቃዋሚ ቡድኖች ሰብስባ “ ይኸው ሰው መልሶ ደግሞ እንዳለው „…አስታጥቃ፣ ቀልባ – ቆርጣ፣ አልብሳ፣ በሉ እንግዲህ ኤርትራን ከዛሬ ጀምሮ መርቄ ሰጥቼአችሁዋላሁ ብላ የእነሱን ጉንጫቸውን ስማ አትሸኛቸውም።“ ለምን ብላ? ይላል ይኸው ሰው ቀጥሎ?
እንግዲህ ኢትዮጵያ፣ በዚያውም ኤርትራ ዛሬ የማን ናት?
በጠበንጃ ኃይላቸው ምርኮኛ ያደረጉዋት አገር ናት? ወይስ ይህች አገር፣ ምርኮኛ ሁነው … አሁን አፋቸው ተለጉሞ ዝም ብለው የሚገዙ ዜጎች ናት?…
የማን ናት ለመሆኑ ኢትዮጵያ ዛሬ?
በትክክል ለመናገር ከጥንት ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ ዞር ብለን ስንመለከተው፣ ኢትዮጵያ፣ ወደድንም ጠላንም -ይህ ደግሞ የብዙ ሺህ አመት ታሪካችን ነው! – ይህቺ አገር „እኔ ብቻ! “ የሚሉ የቶታሊቴሪያን አስተሳሰብ የሚከተሉ፣ የሚያራምዱ ፈላጭ ቆራጭ ሰዎች „አገር ናት“። የሌላ አይደለችም፤ የሌላም አትምሰላችሁ፤ ይህች አገር የማንም አገር ሳትሆን የእነሱ „አገር ናት።“
ይህ ደግሞ በመጀመሪያ መታወቅ አለበት።
ንጉሦች ሁሉ አለጥርጥር፣ በኢትዮጵያ ታሪክ „እኔ ብቻ“ (አይፈረድባቸውም ?) ዘውዱን ጭኜ ልግዛችሁ ባይ ነበሩ። ባይም ናቸው። ደግሞ ይህን ብለው ገዝተውናል። ከዚህም ተነስቶ አንድ ንጉሥ የገዛ ወንድሙን ፈርቶ፣ እሱንም ጠርጥሮም፣ ሊገድለውም ይችላል። በታሪካችን እንደምናውቀው ብዙው በዚህ መንገድ ሞቶአል።
የሃይማኖት አባቱም ሳይቀር እንደዚሁ ያደርጋል። ቀሳውስቱም ካህኑም አስፈላጊ ከሆነ ጓደኛውን፣ አብሮ አደጉን መርዝ በጥብጦም ያጠጣዋል። አጠጥቶታል።
መሣፍንቱና መኳንንቱ „እኔ ብቻ!“ በሚለው ፍልስፍነው፣ በግዛቴ አትድረስብኝ ባይ ነው። አለበለዚያ ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት ብሎ ጦርነት ይገጥማል። ሌላው ቀርቶ በሴት ልጁ ወይም ወዳጁ „ተዋረድኩ“ ብሎ ፊልሚያም ይገጥማል። ደግሞ አድርጎታል። ጦርነት ሁሉ ከየት መጣ ይመስላችሁዋል ?
ግን ! እነሱ እንኳን ቢሆኑ በትንሹም ቢሆን አውቀውበት (ይህ ደግሞ ቀላል እርምጃ አይደለም) ብዙ ንጉሦች ፈቅደው „አንድ ንጉሠ-ነገሥት „ በብዙ ንጉሦች“ ላይ ሹመው ተራቸውን ጠብቀው ለተወሰነ አመታት ተቻችለው አብረው ኖረዋል። አንዱ ሲሞት ጦራቸውን መዘዋል።
ሌላው ክፍል እንዳይበጠብጥም „…ቀኝ አዝማች፣ግራ አዝማች፣ ብላቴን ጌታ፣ ፊታውራሪ፣ ደጃች፣ ራስና ራስ ብተወደድ፣ ልዑል ራስና …ሴቶቹም የቀኝ ባልቴት የግራ፣ እመቤት ሆይ…“ ተባብለው እነሱም ደረጃቸውን እየጠበቁ እንደዚሁ አብረው „ተቻችለው“ አንድ ላይ ኖረዋል። አለበለዚያ የኢትዮጵያን አንድነት መረዳት አይቻልም።
ወታደሩም መቶ አለቃ፣ ሻምበል፣ ሻለቃ፣ ኮነሬል፣ አየተባለ አብሮ ከላይ ወደታች „ተቻችሎ“ ክብሩንና ድንበሩን ጠብቆ አንድ ላይ መኖሩን መርጦአል። ደግሞም አንድ ላይ ኑሮአል።
ካህኑም፣ የሞስሊሙም ሱልጣን፣ …ጭቃ ሹሙም፣ ምስለኔውም….በየደረጃው ተቀምጦ ጊዜውን በመከባበር አሳልፎአል። ይህም ዘዴ እሰከ 20ኛ ክፍለ- ዘመን ድረስ አጅቦናል።
ይህ የፖለቲካውንም የኢኮኖሚውንም፣ የመሬትና የጫካ ሐብቱንም ያጠቃልላል።
በሁዋላ እንግዲህ ማርክስ የሚባል ሰው የወረወረው ትምህርት አገራችን ይገባል። ሌኒን ተከትሎት፣ ስታሊን ተደርቦበት፣ “…እኩልነትና ዲሞክራሲ የኮሚንዝም ሥርዓት እናመጣላችሁዋልን„፣ የሚለው ትምህርታቸው የተማሪ ጆሮ ይገባል። ፍልስፍናቸው በአጭሩ ለመተረክ ሁሉንም ሰው ይሳክራል።
የማርክስ ትምህርት፣ ኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ዓለምን አዳርሷል።
በያለበት ሁሉም ተነስቶ፣ የላይኞቹን ገልብጠው የእራሳቸውን „አምባገነን ሥርዓት“ በገበሬውና በላብ/ወዝ አደሩ ስም መሰርተው፣ ዘርግተው ማን ይናገራቸው፤ አዲስ „ንጉሥ፣ አዲስ መሣፍንት፣ አዲስ መኳንንት… “ ሁነው በየቤተ መንግሥቱ ገብተው „ጭፍሮቻቸውን“ ጄኔራልና ኮነሬል ብለው ሸልመው፣ አልብሰው፣ አልበቃ ብሎአቸው፣ ሥልጣኑን ለልጅ ልጆቻቸው (ኮሪያንና ቻይናን ራሻን ተመልከት) ማውረሰ ነውር ሳይሆን፣ በ20ኛውና ዛሬም በ21ኛው ክፍለ-ዘመን ጌጥ አድርገውታል።
የወይዘሮ አዜብ፣ ለመንፈቅ፣ ለስድስት ወር ያህል „ቤተ-መንግሥቱን ለቅቄ አልወጣም „ የማለቱ ብጤ እንኳን፣ ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነው። የኢህአዴግ የአርባና ሃምስ ዓመት ፕላንም ከዚሁ ጋር በጥብቅ የተሳሰረ ነው፣ ማለትም ይቻላል።
ከሁሉም ግን፣ በብሔር /ብሔረሰብ፣ በነጻ- አውጪዎች ስም በኢትዮጵያ ውስጥ የተከፈተው ጦርነት ሌላ ነገር ሳይሆን እንደ አባቶቻቸው ወይም እንደ ጌቶቻቸው „የመሣፍንት ግዛት“ በየመንደራቸው ለመመሥረት የተነሱ ልጆች ሥራ ነው። ለዚህ ደግሞ እንደ ስታሊን ትምህርት የአመቸ ፍልስፍና የለም።
ይህ ደግሞ እንግዲህ የአዲሱ አምባገነኖቹ „ …የኦሪየንት ሰዎች“ (ምንም እንኳን ካርል ማርክስ በጀርመን አገር ቢወለድም ) በጭቁኑ ሕዝብ ስም የሚያራምዱት በመጀመሪያ በድብቅ በሁዋላ ይፋ የሆነው፣ የአንድ ሰው፣ የአንድ ፓርቲ፣ የአንድ የታጠቀ ጦር ሠራዊት፣ የስለላ ድርጅትና የፖሊስ…. የአምባገነኖች የዕድሜ ልክ ሥርዓት (የፈለጉትን ሽፋን ፈልገው ይስጡት) አገዛዝ ነው ።
አንድ ዕብድ፣ (ሒትለርንና ሞሶሊንን መውሰድ ይቻላል) አንድ ክፉ ጨካኝ ሰው፣ (ስታሊንና ማኦን፣ ኢዲ አሚንና ቦካሳን መጥቀስ ይቻላል)፣ አንድ ሲሾፓት፣ ወይም አንድ አረመኔ (እነ መንግስቱ ኃይለ ማሪያምንና እነ ኪም ኢል ሱንግን መቁጠር፥ አይከብድም) በኮሙኒዝም ወይም በፋሺዝም ስም፣ ወይም በዘውድ ሽፋን፣ አንድ ሰው ሥልጣን ላይ ወጥቶ መዕከላዊ ኮሚቴውን፣ ወይም ካቢኔውን እንደ እንዝርት እያሽከረከረ „የፈለገውን እርምጃ“፣ እሰከ መግደል ድረስ በአንድ አገርና ሕዝብ ላይ ሲወስድ ምንም ዓይነት የመቆጣጠሪያ ዘዴና ይህን የማገጃ ብልሃት ሕዝቡ፣ ነዋሪው፣ አገሩ በእጁ ሳይኖረው ሰለባና ምርኮኛ ሆኖ ዘመን አስቆጥሯል።
ለዚህ ችግርና ጥያቄ ደግሞ „ማርክሲዚም፣ ኮሚኒዝም“ „ፋሺዝም፣ ናሲዮናል ሶሻሊዚም“ እራሱ „የፈላጭ ቆራጩ የዘውድ አገዛዝ“፣ እነዚህ ሁሉ ምንም መልስ እስከ ዛሬ ድረስ ፈልገው ለእኛ አላቀረቡም። ለመስጠትም አልቻሉም። አልሰጡም። ችግሩም ያለው እዚያ ላይ ነው። ግን ደግሞ የሌለ ዕውቀት ከዬት ይመጣል?
ስታሊን ሊጨፍር የቻለው፣ መንግሥቱ ኃይለማሪያም ሊደነፋ፣ ሆኔከር ሊፎክር፣ ኢሳያስ ሊቀባጥር፣ ካስትሮ ሊያጓራ….እረ ስንቱ፣ ሂትለርና ሞሲሊን፣ ግራዚያንና ሆዶጂያ፣ ማኦና ….ኪም፣ እነዚህ ሁሉ ትንሽ ይሁኑ ትላልቅ አጋንንቶች የልባቸውን አለቁጥጥር በአንድ አገርና በአንድ ሕዝብ ላይ ላይ ያን ሁሉ በደልና ግፍ ሊያደርሱ የቻሉበት ምክንያት በአንድ አቢይ ነገር የተነሳ ብቻ ነው።
እሱም፣ እነሱን የሚቆጣጠር አንድ አካል፣ አንድ ነጻ-ተቋም፣ አንድ ነጻ-ፕሬስ በአለመኖሩ ነው።
ግን ደግሞ አስተዋይ ሰው እዚህ ላይ እንደሚገነዘበው፣ እንደተገነዘበው ከዚህ መዓት መውጭያ ሌላ ግሩም የሆነ አማራጭ መንገድ አለ።
አሁን እንግዲህ „ለመሆኑ ኢትዮጵያ የማን ናት?“ የሚለውን አስቸጋሪ ጥያቄ ለመመለስ የተቃረብን ይመስለናል። ደግሞም ተቃርበናል።
እሱም እንደገና አሁንም አንድ አስተዋይ አንባቢ እንደሚረዳው „የማርክስና የሌኒን የስታሊንና የማኦ ወይም የሆድጃ“ ወይም ደግሞ „አልቅሱልኝ“ የሚለው „የኪም ልጆች፣ የኦሪየንቱ ፍልስፍና መንገድ“ ያ! አንድ ፓርቲ፣ አንድ መሪ፣ አንድ ሰራዊት፣ አንድ ጋዜጣ፣ አንድ የስለላ ድርጅት… ምንም ዓይነት መልስ ለገባንበት ችግር እንደማይሰጥ ተገንዝበናል።
የእነሱ የአምባገነኖች መልስ ጥይት፣ እሥራት፣ የሰበአዊ መብት ረገጣ፣ ክትትል፣ ፍጅት፣ ጦርነት እንደሆነም ተገንዝበናል።
ታዲያ አማራጩ መንገድ ምንድን ነው?
አንዴ በአእምሮ መጽሔታችን ላይ እንዳነሳነው „ የብረሃኑ-ዘመን“ የሚባለው „የጸጋ ልጆች ትምህርት“ የሚለውን መጠሪያ ስም የሰጠነው፣ በሌላ ቋንቋ „የኢንላይትመንት ጎዳና“ የተባለው እሱና እነሱ የሚከተሉት ፍልስፍና፣ እነሱ የሚያስተምሩት ትምህርት፣ እሱ ከገባንበት መጨረሻ የሌለው አዙሪት ለመውጣት አማራጭ የሌለው መፍትሔ ነው።
ምን ይላሉ እነዚህ ፈላስፋዎች?
መንግሥት፣ ማንኛውም መንግሥት (ሰብስበን ነው፣ ሁሉንም ጨፍልቀን ነው የምናስቀምጠው፣ የዘውድ አገዛዝ ይሁን የኮሚኒስቶች አምባገነን ሥርዓት፣ የፋሽሺቶች ይሁን የሃይማኖት ሰዎች፣ የነጻ- አውጪዎች ይሁን የወታደሮች፣ እራሱ የምዕራቡ የዲሞክራቶችም መንግሥት ይሁን….ወይም ሌላ ስማቸው ወሳኝ አይደለም) ከአንድ ተራ ሰው፣ እሱ ከአለው አቅም ጋር እነሱ፣ እነዚህ መንግሥታት የያዙት የጨበጡት፣ የመሰረቱት የተከሉት ተቋሞች፣ አካሎች፣ አንድ ተራ ሰው ( እኛ ስለ ግለሰብ ነው የምናወራው) እሱ ከአለው ኃይልና ጉልበት ጋር የእነሱን ሥልጣን መብት ከእሱ ጋር ስናወዳድርና ሲናነጻጻር፣ ያ! ግለሰቡ በእጁ ላይ ያለው የመብቱ እራሱን ከመንግሥት ተጽዕኖ የሚከላከልበት „መሣሪያው“ ይህ ነው ተብሎ የማይነገር ኢምንት ነገር ነው። ምንም ነገር በእጁ የሌለው ምስኪን ደሃ ነው።
የሁለቱን በአንድ ዓይን ማየት አንችልም። ምክንያቱም የአንድ መንግሥትና የአንድ ግለሰብ ጥንካሬና ጉልበት፣ እንደ ሰማይና ምድር የተለያዩ ናቸው።
ሥልጣን ላይ የተቀመጡት (ስማቸው ወሳኝ አይደለም) እነሱ ኃይለኛ እና ጉልበተኞች ናቸው። ወታደሩን ብናይ በሙሉ የእነሱ ናቸው:- የጦር ሰራዊቱ፣ የባህርና የአየር ኃይሉ፣ ፖሊሱና የጸጥታ ክፍሉ በእጃቸውና በደጃቸው ነው።
ነገ ተነስ ብለው ጦራቸውን አውጀው እንድን ደካማ ተራ ሰው ሊደፈጥጡት ይችላሉ።
በዚያ ላይ ፍርድ ቤቱ የእነሱ ነው። ሪዲዮና ቴሌቪዢኑ፣ የመንግሥት ጋዜጣ፣ ቀስቃሹ፣ አደራጁ፣ የሐሰት ወሬ አናፋሹ፣ የካድሬ መፈልፈያ ትምህርት ቤቱ፣ …በተጨማሪ እንደዚሁ በእጃቸው ነው። መንግሥት በየቀኑ የሚበትነው ገንዘብ አለ። ቤት ሰብሮ ሊገባ ይችላል። ….ስልክ መጥለፉ፣ ፖስታ ማፈኑ፣ ኢንተርኔት መዝጋቱ፣ ….ማስፈራራቱ፣ ማሰሩ፣ ማሳደዱ፣ …ከነዚህ ሁሉ ነገሮች ተነስተው፣ የኢላይትመንት ፈላስፋዎች ( የሲ አይ ኤ ን፣ የኬጂብንና የስታሊን የስለላ ፊልሞች ተመልከት) ድሮም ዛሬም (እንደገና የኤድዋርድ ስኖውድን ሰነዶች አገላብጥ) አንድ ተራ ሰው፣ ይህን ሁሉ መንኮራኩር ከሚያንቀሳቅስ ከአንድ መንግሥት ጋር ሲነጻጸር፣ ትንሽ „ፍጡር፣ ትንሽ ትንኚ፣ አቅም የሌለው ትል ነው፤ ይላሉ። “ ይህም እንደሆነ ደግሞ በየቀኑ መገንዘብ ይቻላል።
የኢላይትመንት ፈላስፋዎች ስለ እንደዚህ ዓይነቱ ሁኔታና ስለ እንደዚህ ዓይነቱ ሰው መብት ሲያጫውቱ „ የግለሰብ መብት በሕብረተሰቡ ውስጥ፣ ወይም በአንድ መንግሥት ሥር „ እያሉ ጉዳዩን ይተነትኑታል፤
የሕግ አዋቂዎችና የሕግ አርቃቂዎች፣ የሕገ-መንግሥቱ የበላይ ጠባቂ ዳኞችም፣ እንደ ፈላስፋዎቹ ከግለሰብ መብት ተነስተው „ የግለሰብ ሰበአዊ መብቶችና ክብሩ…“ ብለው ጉዳዩን አስቀምጠው ይዘረዝሩታል።
እንግዲህ ይህም የሆነበት፣ ይህም የተደረገበት ምክንያት አለው፤ ይላሉ።
አንደኛው ምክንያት:- ምንም እንኳን በእግዚአብሔር አምሳል ሰው ሆነን ብንፈጠርም እያንዳዳችን፣ አንዱ ከአንዱ ልዩና ፍጹም፣ እንደ የእጅ አሻራችን -ነጮቹ ይህን „ዩኒክ“ይሉታል- „የተለየንና፣ የተለያየን ነን። “ በመሆናችን ነው።
በመለያየታችንም የተለያየን ልዩ „ዩኒክ“ ግለሰብ በመሆናችንም – ይህ ነው ሁለተኛው ምክንያት- የግለሰብ ነጻነት ሳያከብሩ በድፍኑ፣ በጋሪዮሽ „ …የትግሬ ወይም የሓማሴን፣ የአማራና ኦሮሞ፣ የሴቶች …መብት“ ብቻን በማወጅ „ዲሞክራሲ“ አለ ብሎ አታሎ ማለፍ እንደማይቻልም ለማሳየት ነው።
ይህም በመሆኑ እንግዲህ የብዙ አገሮችን ሕገ-መንግሥት ለማገላበጥ ጊዜ ከአገኘን፣ አዚያም ውስጥ የምናገኛቸው ጉዳዮች አብዛኛዎቹ በመጀመሪያ፣ ይህን በደንብ እንድገመው፣ በመጀመሪያ ደረጃ እነሱ የሚያተኩሩት በግለሰብ ነጻነት፣ በእሱም ላይ ነው።
የግለሰብ፣ የአንድ ዜጋ ነጻነትና መብት ደግሞ፣ ከአልተጠበቀ፣ ከአልተከበረ፤ በሕግ ተደንግጎ ከአልተቀመጠ፣… ያ ሰው ፥ ያ ግለሰብ ደግሞ ደፍሮ መናገር፣ መደራጀት፣ መጻፍ፣ መሰብሰብ፣ ሐብት ማፍራትና ማካበት፣ መመራመርና መፈላሰፍ፣ የፖለቲካ ዓለምም ውስጥ መግባት አይችልም።
ነገሩ ከዚህም አልፎ ይሄዳል። በአንድ ድርጅት ሥር የተደራጀው አንድ ግለሰብ ይህ መብቱ ከአልተጠበቀ፣ ነገ „…አንጃ፣ ሰላይ፣ ከዳተኛ፣ አድርባይ „ በገዛ ጓደኞቹ ተብሎ „ተከሶ“ የሞት ፍርድ ወይም የስም ማጥፋት ዘመቻም እንዳይፈረድበትም እንዳይለቀቅበትም የግለሰብ መብቱና ነጻነቱ እሱን ይጠብቀዋል።
ለዚህኛው ለግለሰብ ነጻነትና መብት „በኢላይትመንት ፍለስፍናና አመለካከት“ ላይ ተመርኩዘው የኢትዮጵያ ምሁሮች በአለፉት ሃምሳና ስድሳ አመታት ይህን ጉዳይ አላነሱም። ሊያነሱም አልፈለጉም። ይህም ምክንያት አለው።
ባለማወቅ ነው እንዳይባል፣ በኢትዮጵያ ሕዝብ ገንዘብ በደንብ ብዙ አገሮች ተልከው ተምረዋል።
የተማሩት ግን ሌላ ነው። በጠቅላላው የፖለቲካ „መደብና ክፍሉ“ ወታደሩም ጭምር፣ ያው ለዚያች „ለእኔ ብቻ „ ከሚለው የአምባገነኖች የፖለቲካ እሩጫና ከቀድሞ መሣፍንቶቹ ከተወረሰው አስተሳሰብ፣ በዚያም ትምህርት ከመማረክ የመጣ ነው ። እኛም እንደ፣ አንዳንዶቹ እንዳሉት፣ „ እንደ ራስ እገሌ፣ ወይም እንደ ሌሊንና እስታሊን ራዕይ …አለን“ ከሚለው ጭፍን ምኞትና ሕልምም የፈለቀ በመሆኑ ነው።
ለዚህ ነው ፕሮግራማቸውም ውስጥ ከአለ „…. የላብ አደሩ/ወዝአደሩ ሠራተኛውና ገበሬው አምባገነን መንግሥት፣ ከአለ …ኤርትራው፣ ትግሬው፣ ጉራጌው፣ ኦሮሞ፣ ኦጋዴን፣ አማራው፣ አፋሩ …መብትና መብቶች፣ እሰከ መገንጠል ድረስ…“ የሚባሉ ነገሮችም የሰፈሩት። እንዲሰፍሩም የተደረጉት።
ግን „በሕግ ፊት እያንዳንዱ ዜጋ፣ እያንዳንዱ ግለሰብ እኩል ነው“፣ ከተባለ፣ „ ማንም ሰው የማንንም ሰው መብቱንና ክብሩን መርገጥ፣ መግፈፍም አይችልም …“ ተብሎ በሕግ ከተደነገገ፣ እነዚህ የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉ ይህን መረሓ ግብር እኩል ከተቀበሉ፣ ነገ ከያዙት የድርጅት ሥልጣናቸው፣ በሌላው „በምርጫ“ ተገፍትረው፣ እንድ ቀን ተሸንፈው እንደሚወድቁ እነሱ በደንብ ያውቁታል። ይህን ስለሚያውቁ ( ይህ ነው ቁልፉ ነገር) ነ ው፣ አንድም ድርጅት „ስለ ግለሰብ ሙሉ ነጻነት „ አንዱ እንዳለው „ጨርሶ ማንሳት የማይፈልጉት“።
ሁሉም የግለሰብ ነጻነቱን ከአወጀ „ዲስፕሊን አይኖርም„ ብለው የሚርበተበቱት።
ግን ደግሞ አንድ አገር „በጥቂት ሕዝብ ተመርጠውም ይሁን ወይም ሳይመረጡ ሥልጣኑን የጨበጡ፣ የቡድኖች የፓርቲዎች…“ አገር ሳትሆን የሁሉም፣ የአገሪቱ ነጻ ዜጎቹዋ አገር ናት።
ይህም ማለት በሌላ ቋንቋ የእኔና የአንተ፣ የእሱዋና የእሱ፣ አጠገባችን ያለውና እሩቅ ቦታ የሚገኘው ዜጋ፣ እኩል፣ መብቱ ተጠብቆለትና እኩል መብቱና ኃላፊነቱ ተከብሮለት፣ በጋራ አንዱ አንዱን በሕግ ፊት ሳይበልጠው የሚጋረው አገር ማለት ነው።
አሜሪካ የማንናት ስንል የምናገኘው መልስም ይህንኑ ነው።
*
ጀርመንስ (ለምሳሌ ያህል ዘርዘር አርገን ብናየው!) ?
ጀርመን የማንናት ብለን ታሪኩዋ ውስጥ ገብተን ስንመለከተው ደግሞ የተለያዩ መልሶችን እንደ ጊዜውና እንደ ሁኔታው፣ እንደ ክፍለ-ዘመኑም እናገኛለን።
እስከ 1918 እአአ ድረስ ይህች አገር የንጉሠ ነገሥቱን የዘውድ አገዛዝ እሰከጣለች ድረስ (ምንም እንኩዋን የፖለቲካ ፓርቲዎችና ነጻ-ጋዜጣዎችም ያኔ ቢኖሩም) የንጉሡ፣ የመኳንንቱና የመሣፍንቶቹ፣ እንዲሁም የከበርቴዎች አገር ነበርች።
ከዚያ በሁዋላ፣ በአዲስ፣ የግለሰቦችን ነጻ-ነት በሚያውቀው ሕገ-መንግሥት ሪፐብሊክ ትሆናለች። የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች እርስ በራሳቸው ሲበጣበጡና አንዱ ሌላውን እየደናቀፈ ሲጓዙ፣ ሁለት ኃይሎች ብቅ ብለው ሥልጣኑም፣ አገሪቱም፣ መሬቱም ሐብቱም፣ ጊዜውም “ ለእኔ ይገባኛል „ ብለው „ይተናነቃሉ።“
ሒትለር ሥልጣኑን ለብቻው ነጥቆ „ሸንጎውን አቃጥሎ“ ፓርላማውን በትኖ፣ ሁሉንም አስሮ „እንድ ፓርቲ፣ አንድ መሪ፣ አንድ አገር፣ አንድ ሠራዊት… የነጮች በላይነት“ ብሎ ዓለምን ለመግዛት ይነሳል።
ጀርመን የማን ናት?
ለሚለው ጥያቄ ያኔ መልሱ ግልጽ ነው። የሒትለርና የፓርቲው፣ እሱም ያዋቀረውና በበላይንት እሱ የሚመራው የጦር ሠራዊቱና የፖሊሱ፣ የስለላ ድርጅቱ፣ ሐብትና ንብረት ነበረች። ሆነችም። በሰው ልጆች፣ በሕይወትና በሞት፣ በሰላም በጦርነት ወሳኙ እሱ ሒትለር ሆነ።
1945 ሒትለር ተንኮታኩቶ ይወድቃል።
ጀርመንም ከዚያ በሁዋላ (የሚታወቅ ነገር ነው) ለሁለት ትከፈላለች። አንደኛው ምሥራቅ ጀርመን የኮሚስቶቹ ሌላው ምዕራብ ጀርመን የፓርላማ ሥርዓት፣ የዲሞክራቶቹ አገር ትሆናለች።
እነ ሆኔከርም እን ኡልብሪሽት ኮሚኒስቶቹም የእራሳቸውን ግዛት (እንዲያው ለማስታወስ ያህል) „የጀርመን ዲሞክራቲክ ሪፓብሊክ „ ብለው (ማንን ለማታለል) ይጠሩአት ጀመር ።
እንደሚታወቀው፣ ይህ ሥርዓት፣ ከዲሞክራሲ ሥርዓትና የአኗኗር ዘይቤ ጋር ምንም የሚያገናኘው፣ የለየላቸው የአምባገነኖች ግዛት ነበረች።
ጀርመን ለመሆኑ የማን ናት?
ጀርመን ከተከፈለች በሁዋላ እላይ በጥቂቱ ለመግለጽ እንደሞከርነው- መልሱ ግልጽ ነው።
የኮሚኒዝም ሥርዓት በምሥራቅ አውሮፓ፣ አንድ በአንድ፣ ተራ በተራ ተንኮታኩቶ ሲወድቅ ደግሞ ጀርመን እንደገና ትዋሃዳለች።
አሁን ጀርመን የማን ናት?
ጀርመን ዛሬ የሁሉም ልጆቹዋ፣ የዜጎቹ አገር ተመልሳ እንደገና ሆናለች። ይህ ሲባል በዚህች አገር ኮሚስቶችና ፋሽሽቶች፣ ጨርሶ የሉም ማለት አይደለም። ተደራጅተው አሉ። እንዲያውም በሌላ ስም አንዳንድ ቦታ ተመርጠው ሸንጎ ውስጥ ገብተው ቦታቸውን ይዘው ይከራከራሉ።
ትልቁ የጀርመን ፓርላማ፣ በበርሊኑ በቡንደስ ታግ ውስጥ የቀድሞ ኮሚኒስቶች „ዲ-ሊንከ“ የሚባሉት ማለት „ ሌፍቲስቶቹ“ ስማቸውን ቀይረው ወንበራቸውን ይዘው ይሟገታሉ። ግን ከአምባገነንነት አቋማቸው ተገላግለው በአዲስ የወሃ ጠበል „ተጠምቀው“ የቀድሞ ሥራቸውን አውግዘው „ዲሞክራት „ ሁነው ይንቀሳቀሳሉ።
አሁን ያቺ አገር ከምስራቁ የአውሮፓ አህጉር ጋር፣ ከኮሙኒዝምና ከፋሽዝም ከዚያ የመከራ ዘመን በሁዋላ „ነጻ-ሰውና ነጻ-ሕዝብ፣ ነጻ -ሕብረተሰብና፣ ነጻ- ሥርዓት፣ ነጻ- ፓርላማ ወይም ሸንጎ፣ ነጻ-ፕሬስና ነጻ …ነጻ…“ የሚባሉት ቃላቶችና ፍልስፍናዎች፣ እነዚህ የኑሮ ዘይቤዎች፣ ማንም የማያግዳቸው ዓለም አቀፋዊ መብቶች ሁነዋል።
(የምናወረው አሁን ስለ መብት ጉዳይ እንጅ፣ ስለ ኢኮኖሚ አይደለም። የኢኮኖሚ ጉዳይ ከተነሳ ደግሞ የግል ሐብት በሕግ የታወቀበት አካባቢ ነው። )
የተለያዩ ኃይሎች እኩል የሚተዳደሩበትና እኩል እነሱ፣ አንዱ ከአንዱ ሳይበልጥ የሚስተናገዱበት (ቁም ነገሩ ያለው እዚህ ላይ ነው)፤ የፖለቲካ ጨዋታቸውን መልክ የሚሰጥ፣ የሚያረጋግጥ ኃይል ማነው ? ቢባል፣ እንደሚባለውና ማርክስ እንደሚያስተምረው „የከበርቴው መደብ „ ሳይሆን ጠቅላላው የሕብረተሰብ ክፍሎች፣ እነሱ ተስማምተው ያወጡት ደንብና ህግ ነው። ይህም አንዱን ከአንዱ የማያስበልጠው „ሕገ-መንግሥት“ ዓለም አቀፋዊ የሆኑ አንቀጾችንም አዝሎአል።
ምንድን ናቸው፣ ይህ „ሕገ-መንግሥት“ የሚያነሳቸው ነገሮች? ምን ዓይነት ዓለማቀፋዊ ፍሬ ነገሮችን ነው ያዘለው?
እንግዲህ አንቸኩል ከተባለ „ስለ ፍርድና ፍትሕ“፣ ስለዓለም አቀፉ የሰበአዊ መብቶች አዋጅ፣ ቀስ ብለን ደግመን፣ ደጋግመን እንደገና እንመጣበታለን ።
ከዚያ በፊት ስለ ነገሮች ሁሉ እምብርት ስለ ፕሬስ ነጻነት ቀጠል አድርገን እንመለከታልን።
ስለ የግል ሐብትም፣ አሰፈላጊነት እናነሳለን።
*
እንግዲህ ተፈጥሮ በሰጠን አፋችን መናገር እንችላለን። ማሰብ በምንችልበት አእምሮአችን ማንም፣ ምንም ሳያግደን ማሰብም፣ እያንዳዳችን እንችላለን። ሕሊና በሰጠን ፍርዳችን ማንኛችንም ክፉና ደጉን ለይተን ለመፍረድ፣ አንተም አንቺም፣ …ሁላችንም ችሎታ አለን። መጻፍ በምንችልበት ፊደላችን ነጻ -ሓሳባችንን ማንንም ሳንፈራ መጻፍና ማሰራጨት እንችላለን።
ይህን ከእግዚአብሔር የተሰጠንን ጸጋ ደግሞ ደግሞ ለመናገር፣ ማንም ሰው ሊያግደው አይችልም።
ስለዚህም ደግመን ከሌላ አቅጣጫ ወደፊት እናነሳለን።
ኢትዮጵያ የማን ናት? ለሚለው ጥያቄ መልሱ (ያቺ አገር ኤርትራም ጭምር) የግለሰብ ነጻነትን የሚያምኑ የሰበአዊ መብቶችን የሚያከብሩ የነጻ ሰዎች፣ የነጻ-ዲሞክራቶች፣ የነጻ-ዜጎች አገር ናት።
ይህን ለማጠቃለል፣ መሆን ያለበት መልስ ይኸው ነው።
ይህ መሆን ሲገባው ግን፣ በሌላ በኩል ኢትዮጵያ የማን ናት? ሲባል የምናገኘው የዛሬው ሥዕል ሌላ ነው።
በሌላ በኩል ያቺ አገር ዛሬ የምርኮኞችና ጠበንጃ የያዙ ሰዎች አገር ናት። ዝናር የታጠቁና የሚያስፈራሩ ወታደሮችም አገር ናት። ኢትዮጵያ የቴታለቴሪያን አስተሳሰብ የሚያራምዱም ቡድኖች የፈሉባት አገር ናት።
ይህ መቀየር አለበት። ይህ መቀየርም ያስፈልገዋል።
እንዴት የሚባለው ነገር ወደፊት ይነሳል።
ኢትዮጵያ የማንናት? የሚለው ጥያቄ፣ ቀደም ሲል እንዳልነው፣“ አሜሪካ የማናት?“ ከሚለው የደፋር ጥያቄ በምንም አይለይም። ጀርመን የማን ናት ከሚለውም ጥያቄ አያንስም።
በያዝነው በጥያቄም ሆነ በመልስ ፍለጋውም ላይ „ኢትዮጵያ የማን ናት“ ብለን የኢንላይትመንት ሰዎችን ጥያቄ ሳንጥለው ወደፊት እንቀጥልበታለን።
ይልማ ኃይለ ሚካኤል
______________________________________________________________